የደብረ ብረሃን ዩኒቨርስቲ የባህል፣ የታሪክና የቋንቋ ማዕከል እንደገና መደራጀትን አስመልክቶ የተሰጠ መግለጫ

News

የደ/ብርሃን ዩኒቨርሲቲ ከተቋቋመበት 1999 ዓ.ም ጀምሮ በተለያዩ የሙያ መስኮች ብቃት ያላቸውን ሙያተኞች በማፍራት ወደ ስራ ገበያው በማስገባት ለአገራችን ሁለንተናዊ ዕድገት በሚደረገው ጥረት የበኩሉን ድርሻ እየተወጣ ከመሆኑም ባሻገር በጥናትና ምርምርና በማሀበረሰብ አገልግሎትም ቀላል የማይባል ተግባራትን እያከናወነ ይገኛል:: በተለይም ደግሞ በተጠና እና ተጨባጭ ለውጥ በሚያመጣ መልኩ ዩኒቨርሲቲው የሚገኝበትን አካባቢ ማሀበረሰብ ተጠቃሚ የሚያደርጉ በርካታ የማህበረሰብ አገልገሎቶችን በማከናወን ላይ ይገኛል። ዩኒቨርሲቲው የሚያከናውናቸውን የተለያዩ የማህበረሰብ አገልግሎቶች በዕቅድ፣ በትግበራና በአፈፃፀም ግምገማ ወቅት ከአካባቢው ማህበረሰብ ጋር መድረኮቸን በመፍጠር በስፋት ይመካከራል፡፡ በመሆኑም አብዛኞቹ የማህበረሰብ አገልገሎቶች የአካባቢውን ማህበረሰብ ተጠቃሚነትና ፍላጎት መሰረት አድርገው የሚከናወኑ በመሆናቸው የማህበረሰቡ ግብረ መልስ በአብዛኛው አበረታች ነው።  ሆኖም አልፎ አልፎ አገራዊ አቅጣጫዎችና አካባቢያዊ ፍላጎቶች በመጠኑም ቢሆን ልዩነት የሚፈጥሩበት ሁኔታ መከሰታቸው አልቀረም:: እንደዚህ ዓይነት ሁኔታዎች ሲያጋጥሙ የአካባቢውን ማህበረሰብ ፍላጎት ማዳመጥና ከአጠቃላይ አገራዊ ተልዕኮው ጋር በማይጋጭ መንገድ ማጣጣም አስፈላጊ ነው።

ዩኒቨርሲቲው የሚገኝበት የሰሜን ሸዋ አካባቢ የቱባ ባህል ባለቤት፣ የኢትዮጵያ የረዥም ጊዜ ታሪክና ፖለቲካ ማዕከል እንዲሁም የአማርኛ ቋንቋና ስነፅሁፍ መፈጠሪያ እንደመሆኑ መጠን እነዚህን የማህበረሰብ ህልውና መሰረቶች የዩኒቨርሲቲው ዋነኛ ተግባራት መሆን እንዳለባቸው ከማህበረሰቡ በተደጋጋሚ ጥያቄዎች ሲነሱ አስተያየቶችም ሲሰጡ ቆይተዋል፡፡ በመሆኑም፡-

  1. ካለን ተሞክሮ በመነሳት ከዚህ በፊት የነበረዉን የባህል ማዕከል የበለጠ ለማጠናከርና ለማስፋት ታሪክንና የአማርኛ ቋንቋን በማካተት አንድ ማዕከል ማቋቋም አስፈላጊ መሆኑ ታምኖበት የባህል፣ የታሪክና የቋንቋ ልማት ማዕከል ሆኖ እንደገና እንዲቋቋም ተወስኗል።
  2. የሚቋቋመው ማዕከል ተልዕኮ የአካባቢውን ባህል፣ ታሪክና እና የአማርኛ ቋንቋ ስነፅሁፍ ማስተማርና  ማጥናት ላይ ያተኩራል።
  3. የአማርኛና የታሪክ ትምህርት ፕሮግራሞች ለተማሪ ምርጫ ቀርበዉ ዩኒቨርሲቲዉን ሌጅስሌሽን (Legislation) ላይ የተቀመጡን ዝቅተኛ የተማሪ ቁጥር ማሟላት የሚችሉ ከሆነ በመጀመሪያ፣ ሁለተኛና ሦስተኛ ድግሪ እንዲማሩ ይደረጋል፡፡
  4. ከላይ በተራ ቁጥር 3 በተጠቀሱት ትምህርት ክፍሎች ዉስጥ ያሉ መምህራን ከማስተማር ስራቸዉ ጎን ለጎን የማዕከሉ ተመራማሪ በመሆን ያገለግላሉ፡፡
  5. ማዕከሉ በዳሬክቶሬት ደረጃ የሚቋቋም ሆኖ አንድ ዳይሬክተር እና በስሩ የአማረኛ ቋንቋና የታሪክ ዘርፍ አስተባባሪዎች ይኖሩታል፡፡ 

                                                                                  ደብረ ብርሃን ዩኒቨርሲቲ