በሚል መሪ ቃል የዩኒቨርሲተው ከፍተኛ አመራሮች ተማሪዎች፣መምህራንና የአስተዳደር ሰራተኞች፣የዞን ሴቶች ህጻናትና ወጣቶች መምሪያ ኃላፊዎችና የሊግ ተወካዮች፣በተገኙበት መጋቢት 2 ቀን 2011 ዓ.ም በደማቅ ሁኔታ ተከብሯል፡፡
በበዓሉ ላይ የደብረብርሃን ዩኒቨርሲቲ የሴቶች ህጻናትና ወጣቶች ዳይሬክቶሬት ዳሬክተር ወ/ሮ ኃይማኖት ቢችል እንደገለጹት የሴቶችን ቀን ስናከብር በሴቶች ላይ ይደርስ የነበረውን ጭቆና ለማስወገድ የተደረገውን የትግል እንቅስቃሴና ውጤታማነት ለመዘከር፣ሴቶች ከነበረባቸው ጭቆና ተላቀው በኢኮኖሚ፣በማህበራዊ፣በስነ-ልቦናዊና ፖለቲካዊ እኩል ተሳታፊና ተጠቃሚ የሚሆኑበትን ምቹ ሁኔታ መፍጠር የሚቻልበትን ሁነት ለመዘከር መሆኑን አንስተዋል፡፡እንደ ዳይሬክተሯ ገለፃ በዓሉ ሴቶች ውጤታማ የሆኑባቸውን ስራዎች በመዘከር ለማበረታታት ያስችላል ብለዋል፡፡
የደብረብርሃን ዩኒቨርሲቲ የጥናትና ምርምር ማህበረሰብ አገልግሎት ም/ፕሬዚዳንት ዶ/ር አልማዝ አፈራ በዓሉን በንግግር ሲከፍቱ የሴቶች ተሳትፎና ተጠቃሚነትን ማምጣት ቸርነት አይደለም፡፡ነገር ግን ለአንድ ሀገር ህልውና በመሆኑ አንዱ ሰጭ ሌላው ተቀባይ በሆነ መልኩ ሳይሆን ሰብዓዊ ወይም ሰዋዊ መብትም ጭምር ነው ብለዋል፡፡ፕሬዚዳንቷ አክለው እንደገለጹት ሴት የቤተሰብና የሀገር መሰረት ስለሆነች እኛ የዩኒቨርሲቲው ማህበረሰቦች ከዘር፣ከጾታና ከሀይማኖት አድሎ በጸዳ መልኩ መስራትና መታገል እንዲሁም በግልፅ ብቻ ሳይሆን በረቀቀ ዘዴ ጭምር የሚደረጉ ጾታዊ ትነኮሳዎችን ለመዋጋት መስራት አለብን ብለዋል፡፡
በበዓሉ ላይ ሁለት ጥናታዊ ጽሁፎች የሴቶች ተሳትፎና ተጠቃሚነት እና እናትነት/Motherism/ በሚሉ ርዕሶች በዶ/ር ሰርካለም ይገረሙ እና በመ/ር ጌትነት ጥበቡ ቀርበው ውይይት ተካሂዶባቸዋል፡፡በውይይቱም የቀረቡት ጽሁፎች አስተማሪ በመሆናቸው ለተግባራዊነታቸው ሁሉም አካል ትኩረት ሰጥቶ መስራት እንዳለበት ተጠቁሟል፡፡
በመጨረሻም አርዓያ ለሆኑ ሴት መምህራንና በ2011 ዓ.ም የመጀመሪያው ወሰነ ትምህርት ከ1ኛ-3ኛ ደረጃ ከፍተኛ ውጤት ላስመዘገቡ ሴት ተማሪዎች የእወቅናና የማበረታቻ ሽልማት ተሰጥቷል፡፡ አቶ ደረጀ አጅቤ የአስተዳደርና ተማሪዎች አገልግሎት ም/ፕሬዚዳንት ተወካይ የማበረታቻ ሽልማቱን ከሰጡ በኋላ ባደረጉት የመዝጊያ ንግግር ሴቶች ቤተሰባቸውን ይመራሉ፣ያስተዳድራሉ፤ለዚህም መስዋዕትነት ይከፍላሉ፡፡አመራር ለመሆን ሴቶች ራሳቸው መስዋዕትነት መክፈል ይኖርባቸዋል፡፡ሴቶችን አመራር ስናደርጋቸው ምቹ የስራ ቦታና ሁኔታ ልንፈጥርላቸው ይገባል ብለዋል፡፡