Notice
በዩኒቨርሲቲው የተፈጥሮና ቀመር ሳይንስ ኮሌጅ አዘጋጅነት በማቲማቲካል ሞዴሊንግ የትምህርት መስክ ላለፉት 4 ዓመታት የ3ኛ ዲግሪያቸውን ሲከታተሉ የቆዩት መ/ር ሽመልስ በቀለ፣ መ/ር ተስፋዬ ተፈራ እና መ/ር ጥበቡ ቱሉ የተባሉ እጩ ዶክተሮች ተጋባዥ የዩኒቨርሲቲው መምህራን፣ የኮሌጁ አመራሮችና አማካሪዎች በተገኙበት የመመረቂያ ጹሑፋቸውን በቨርቹዋል ሞዳሊቲ አቅርበው በስኬት ማጠናቀቃቸውን የሂሳብ ትምህርት ክፍል ሀላፊ መ/ር ደጀኔ ሸዋቀና ገልጸዋል፡፡
እንደ ሀላፊው ገለፃ ከሆነ ተማሪዎቹ መውሰድ ያለባቸውን የትምህርት አይነቶች በሚገባ ወስደው ለመመረቅ የሚያበቃቸውን ጥናትና ምርምር አካሂደው በዩኒቨርሲቲው ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ በተሳካ ሁኔታ ያጠናቀቁ እጩ ዶክተሮች መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ ይህም ለዩኒቨርሲቲው ትልቅ ስኬት ነው ብለዋል፡፡ ደብረ ብርሃን ዩኒቨርሲቲን ከአቻ ዩኒቨርሲቲዎች ተመራጭና ተወዳዳሪ ማድረግ፣ ዩኒቨርሲቲውን በጥሩ መልክ የማስተዋወቅና ገጽታ መግንባታ፣ በሀገር ውስጥና በውጪ ሀገር ከሚገኙ ምርጥ ዩኒቨርሲቲዎች ጋር በጋራ ለመስራት ያስችላል ነው ያሉት፡፡
በመጨረሻም ፕሮግራሙ እንዲሳካ አስተዋፅኦ ላደረጉ ለዩኒቨርሲቲው አመራሮች፣ መምህራን፣ የአይሲቲ ባለሙያዎችና የመብራት ሰራተኞች ላቅ ያለ ምስጋና አቅርበዋል፡፡