Notice
አዲሱ የትምህርት ዘመን የምንጀምርበት በመሆኑ ከፍተኛ ዝግጅት ማድረግ ያስፈልጋል ብለዋል፡፡
እንደ ዳይሬክተሩ ገለጻ ደብረብርሃን ዩኒቨርሲቲ ብቸኛው ሆስፒታል ሳይኖረው የኮቪድ ህክምና የሰጠ፣ ለለይቶ ማቆያ፣ማግለያና ማከሚያ ሆኖ በመቆየቱ ይህንን ማፅዳትና ወደ ስራ ማስገባት ያስፈልጋል፡፡በአሁኑ ሰዓት ተገልጋዮች/ታካሚዎች ወደ ሌላ ቦታ እንዲዛወሩ በማድረግ ህጋዊ ፍቃድ ከተሰጠው ድርጅት ጋር ውል በመግባት የማጽዳት /Disinfect/ የማድረግ ስራ እየተሰራ መሆኑን አስረድተዋል፡፡በዚህም በአለም ጤና ድርጅት የፀረ-ተህዋሲያን ርጭት መመሪያና በጤና ባለሙያዎች ምክረ-ሀሳብ መሰረት ሁሉም የተማሪ ማደሪያ ህንጻዎች፣ምግብ ቤቶች፣ጤና ጣቢያ፣ሁሉም አገልግሎት ሲሰጥባቸው የነበሩ ህንጻዎችና ቢሮዎች ሙሉ በሙሉ እንዲረጩና እንዲጸዱ እየተሰራ ነው ብለዋል፡፡ማደሪያ ህንጻዎቹን፣መማሪያ ክፍሎቹን ቀለም የመቀባት ስራዎች ፣የምግብ ቤት ቁሳቁሶች ግዥና የተለያዩ ጥገናዎች እየተሰሩ ይገኛሉ፡፡ለዚህም ዩኒቨርሲቲው ከ43 ሚሊዮን ብር በላይ በጀት መድቦ እየተንቀሳቀሰ ነው፡፡
አቶ አለምነው መልካሙ እንዳሉት በኳራንታይንና በለይቶ ማቆያ ወቅት ተገልጋዮች ሲጠቀሙባቸው የነበሩ ብርድልብሶችና ፍራሾች ሙሉ በሙሉ በማቃጠል ወይም በመቅበር እንዲወገዱ ተደርጎ በምትኩ በአዲስ 1800 ፍራሾች ተዘጋጅተዋል፡፡እንዲሁም ለመጀመሪያ ጊዜ ሳኒታይዘር፣ሳሙናና ማስክ ለማቅረብ ዝግጅት ተጠናቋል በማለት ገልጸዋል፡፡ከግብዓት አኳያ ተማሪዎችን ተቀብለን ለ3 ወር የሚቆዩና የማይበላሹ የምግብ ግብዓቶችን አዘጋጅተናል ያሉት ዳይሬክተሩ አቅራቢ የሌላቸው አቅራቢ እንዲኖራቸው ተደርጓል ብለዋል፡፡
የተማሪዎችን አቀባበል አስመልክቶ የተቋቋመው የጤና ሰርቪላንስ ቡድኑ የሙቀት ልየታን ጨምሮ ችግሩ ቢከሰት ለይቶ ማቆያ፣ማግለያና ማከሚያ ህንጻዎችን አዘጋጅቶና የሰው ኃይል አሰልጥኖ ወደ ስራ ይገባል ያሉት ዳይሬክተሩ ተማሪዎች፣የተማሪ ወላጆችና ህብረተሰቡ ያለውን ነባራዊ ሁኔታ ተገንዝበው ድጋፍና ትብብር እንዲያደርጉላቸው ጠይቀዋል፡፡በመጨረሻም ተማሪዎች ከወትሮው የተለየና የሁለት አመት ትምህርት በአንድ አመት እንደሚሰጥ አውቀው እራሳቸውን ለኮሮና በማያጋልጥ መልኩና ሰላማቸውን በሚያስጠብቅ ሁኔታ ማጠናቀቅ ይጠበቅባቸዋል ብለዋል፡፡